ቀጥታ, የአሜሪካ ጦር ለሰባተኛ ተከታታይ ምሽት በኢራን ላይ ድብደባ መፈጸሙን አስታወቀ

ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከቴህራን ጋር የተደረሰው የተኩስ አቁም “ማብቃቱን” ካስታወቁ በኋላ የአሜሪካ ጦር ለሰባተኛ ምሽት ድብደባ መፈጸሙን አስታወቀ። የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) በኤክስ ገጹ ላይ ባጋራው መግለጫ ጦሩ “የቅኝት ጣቢያዎችን፣ የወታደራዊ ሎጀስቲክ መሠረተ ልማቶችን፣ ከምድር በታች የሚገኙ የጦር መሣሪያ ማከማቻዎችን እና የባሕር ኃይል አቅሟ” ላይ ድብደባ መፈጸሙን አስታውቋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ዩክሬን በሩሲያ የኦንላየን እቃዎች መሸጫ መጋዘን ላይ ከባድ ጥቃት መፈጸሟ ተገለጸ

    ከሞስኮ በስተደቡብ ምሥራቅ በግምት 475 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው የታምቦቭ ከተማ በሚገኝ መጋዘን ውስጥ ሰባት ሰዎች ሲገደሉ 25 ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል

    የፎቶው ባለመብት, social media

    የምስሉ መግለጫ, ከሞስኮ በስተደቡብ ምሥራቅ በግምት 475 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው የታምቦቭ ከተማ በሚገኝ መጋዘን ውስጥ ሰባት ሰዎች ሲገደሉ 25 ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል

    የዩክሬን ድሮኖች በሩሲያ ግዙፍ የኦንላየን እቃዎች መሸጫ የሆነውን የዋይልድቤሪስ ሁለት መጋዘኖችን መትተው ስምንት ሰዎች መሞታቸውን እና 62 ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን የሩሲያ ባለሥልጣናት ገለጹ።

    ከሞስኮ በስተደቡብ ምሥራቅ በግምት 475 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው የታምቦቭ ከተማ በሚገኝ መጋዘን ውስጥ ሰባት ሰዎች ሲገደሉ 25 ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል።

    በሞስኮ ክልል በኤሌክትሮስትል በሚገኝ ሌላ የዋይልድቤሪስ መጋዘን ውስጥ በተፈጸመ የድሮን ጥቃት ደግሞ አንድ ሰው ሲገደል 37 ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል ተብሏል።

    የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ ጥቃቶቹ "ማዕቀብ የተጣለባቸውን የድሮን እና ለሃሰሳ የሚያገለግሉ መሣሪያዎች ክፍሎችን ለማቅረብ" ጥቅም ላይ የዋሉ "ዋና ዋና የሎጂስቲክስ ተቋማት" ላይ መፈጸማቸውን ተናግረዋል።

    ዩክሬን በአዞቭ ባሕር፣ በጥቁር ባሕር እና በሩሲያ ሥር በምትገኘው ክሪሚያ ውስጥ ዒላማዎችንም መምታቷን አክለዋል።

    መጋዘኑ ላይ ጥቃት ከደረሰ በኋላ የወጡ ያልተረጋገጡ ምስሎች ከአንድ ሰፊ ሕንፃ የእሳት ነበልባል እና ጥቁር ጭስ ሲወጣ አሳይተዋል።

    በርካታ ሰዎችም ወደ መኪና ማቆሚያ ቦታ እየሸሹ ሲሄዱ ታይተዋል።

    ዜሌንስኪ እንዳሉት የዩክሬን እርምጃዎች "የሩሲያ ጦር በሲቪል መሠረተ ልማታችን ላይ እንዲሁም በከተሞቻችንና በማኅበረሰባችን ላይ ለሰነዘረው ጥቃት" ምላሽ የሰጡ ናቸው። ረቡዕ ምሽት ላይ በመላው ዩክሬን በተፈጸሙ የሩሲያ ጥቃቶች 14 ሰዎች ተገድለዋል።

    ዋይልድቤሪስ እንደ አማዞን ያለ ግዙፍ በኦንላየን እቃዎችን የሚሸጥ የሩሲያ ኩባንያ ነው።

    የዋይልድቤሪስ ሥራ አስፈጻሚ ታታይና ኪም ለሩሲያ እና ለኩባንያው “አስቀያሚ ምሽት ነበር” ብለዋል።

    የቴምቦቭ ክልል አስተዳዳሪ ኢቪግኒ ፐርቬሾቭ በቴሌግራም ገጻቸው ላይ “በምሽት ፈረቃ እየሰሩ የነበሩ ሰባት ሰዎች እዚያው ተገድለዋል” ሲሉ ጽፈዋል።

    አክለውም 25 ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል፤ ሰባቱ በከባድ ሁኔታ ውስጥ ናቸው ብለዋል። አብዛኛው ጉዳት የደረሰው በፍንጥርጣሪዎች መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።

    ይህ በታምቦቭ ክልል ላይ የተፈጸመው ጥቃት፣ ጥቅም ላይ በዋሉት ድሮኖች ብዛት እና በደረሰው የሰው ሕይወት መጥፋትና የጉዳት መጠን ሲታይ "እጅግ ትልቅ እና ኢ ሰብአዊ" ጥቃት ነበር ብለዋል።

  2. ኩዌት የኢራንን ጥቃት ተከትሎ በርካታ የእሳት አደጋ ሠራተኞች መጎዳታቸውን አስታወቀች

    ኢራን በኩዌት የኃይል ማመንጫ እና የውሃ ማጣሪያ ላይ በፈጸመችው ጥቃት እሳት ተቀስቅሷልሷል

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu

    የምስሉ መግለጫ, ኢራን በኩዌት የኃይል ማመንጫ እና የውሃ ማጣሪያ ላይ በፈጸመችው ጥቃት እሳት ተቀስቅሷል

    የኩዌት እሳት አደጋ መከላከያ ቅዳሜ ዕለት የተፈጸመውን የኢራን ጥቃት ተከትሎ የተቀሰቀሰ እሳትን ለማጥፋት የተሰማሩ በርካታ ሠራተኞች ጉዳት እንደ ደረሰባቸው አስታወቀ።

    "የመጀመሪያው ክስተት እሳቱን ለማጥፋት ሲጥሩ የነበሩ የእሳት አደጋ ተከላካዮች እና አንድ ሲቪል ሠራተኛ ላይ በርካታ ጉዳቶችን አድርሷል" ሲል ድርጅቱ በመንግሥት ለሚተዳደረው የዜና ወኪል ኩና ተናግሯል።

    ጥቃቱ የተፈጸመበት አካባቢ የነበሩ ሰዎች አካባቢውን እንዲለቅቁ የተደረጉ ሲሆን፣ የቆሰሉት ሰዎች አስፈላጊውን እርዳታ እንዲያገኙ ወደ ሕክምና ተቋም ተወስደዋል ሲል ጨምሮ ገልጿል።

    የኩዌት ኤሌክትሪክ፣ ውሃ እና ታዳሽ ኃይል ሚኒስቴር፣ በኃይል ማመንጫው እና በውሃ ማጣሪያው ላይ ኢራን የፈጸመችወን ጥቃት ተከትሎ እሳት መቀስቀሱን አስታውቆ ነበር።

    አሜሪካ ለሰባት ተከታታይ ሌሊት ጥቃት የፈጸመች ሲሆን ኢራንም በምላሹ የዩኤስ ጦር ኃይል መቀመጫ የሆኑ የቀጣናው አገራት ላይ ጥቃት ሰንዝራለች።

    በዋሺንግተን እና ቴህራን መካከል ዳግም ጦርነት ያገረሸው በፓኪስታን አደራዳሪነት የተፈረመው የሰላም ስምምነት ውድቅ ከሆነ በኋላ ነው።

  3. ኢራን ከአሜሪካ ድብደባ በኋላ በባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት አጠናከረች

    የኢራን ጎዳና ላይ የተሰቀለ የሚሳዔል ምሥል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ቅዳሜ ዕለት ኢራን በባሕረ ሰላጤው በሚገኙ የአሜሪካ አጋር አገራት ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት አጠናክራ መቀጠሏን ሮይተርስ ዘገበ።

    አሜሪካ ለሰባተኛ ጊዜ ትናንት ምሽት በኢራን ወታደራዊ ተቋማት ላይ ድብደባ መፈጸሟን አስታውቃለች።

    በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት ከፈረሰ በኋላ ግጭቱ ተባብሶ ቀጥሏል።

    ኩዌት የውሃ ማጣሪያዋ በኢራን ሚሳዔል የተመታባት ሲሆን አውሮፕላን ማረፊያዋም በተደጋጋሚ በደረሰበት የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃት ስጋት ምክንያት አገልግሎቱን አቋርጧል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ በኩዌት አሪፍጃን የጦር ካምፕ የሚገኝ የአሜሪካ ጦር ድጋፍ ሰጭ ማዕከል ላይ ጥቃት ፈጽሞ የራዳር ተቋምን ማውደሙን አስታውቋል።

    የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን አብዮታዊ ዘቡ በባሕሬን የአሜሪካ ጦር አውሮፕላኖች የተሰባሰቡበትን ሼክ ኢሳ የጦር ሰፈር እና የደኅንነት መረጃ ማዕከልን ማጥቃቱን ዘግበዋል።

    ሮይተርስ የዘገባውን ትክክለኛነት ለማጣራት ያደረገው ጥረት አልተሳካም።

    “የአሜሪካን ጦር ጭካኔ የሚገታ ዓለም አቀፍ ተቋም ስለሌለ፣ ‘ያጠቃችሁን፣ እናንተም በተመሳሳይ መልኩ አጥቁት’ የሚለውን የቁርአን ትዕዛዝ ከመከተል ውጪ ሌላ አማራጭ የለንም" ሲሉ የአብዮታዊ ዘቡ በመግለጫው አስታውቋል።

    ዘቡ በዚህ መግለጫው በአካባቢው የሚገኙ የአሜሪካ አጋሮች ተጨማሪ ጥቃቶች ሊያጋጥሟቸው እንደሚችሉ አስጠንቅቋል።

    አርብ ዕለት ሁለቱም ወገኖች በመርከብ እንቅስቃሴ ላይ ያነጣጠሩ እርምጃዎችን የወሰዱ ሲሆን፤ የአሜሪካ የባሕር ኃይል ወደ ኢራን የሚሄዱ መርከቦችን ያገደ ሲሆን ቴህራን በበኩሏ የዓለምን የአንድ አምስተኛ የነዳጅ አቅርቦት የሚተላለፍበት ወሳኝ የውሃ መስመር ላይ ሕግ የጣሱ ያለቻቸው መርከቦች ላይ ማነጣጠሯን አስታውቃለች።

  4. የዩክሬን መከላከያ ሚኒስትር ከኃላፊነታቸው መነሳት በርካታ ወታደሮችን እንዳስቆጣ ተነገረ

    የዩክሬኑ ፕሬዚደንት እና ሲርስኪ (በስተቀኝ)

    የፎቶው ባለመብት, Ukrainian Presidential Press Service/Handout via Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ሲርስኪ (በስተቀኝ) በ2022 የሩሲያ ሙሉ ወረራ በጀመረበት ወቅት የዩክሬን ዋና ከተማ መከላከያን መርተዋል

    የዩክሬን መከላከያ ሚኒስትር ከኃላፊነት መነሳት በርካታ ወታደሮችን እንዳስቆጣ ተነገረ።

    አንድ ስሙ እንዳገይለፅ የጠየቀ ወታደር ከኃላፊነታቸው የተነሱት ሚኒስትር ካልተመለሱ ሲዋጋላት የቆየው ሁሉም ነገር ከንቱ እንደሚሆን ገልጿል።

    በደረሰበት ጉዳት ምክንያት ቀዶ ሕክምና ለማድረግ ቀጠሮ ላይ የሚገኘው ይህ ወታደር፣ ከማደንዘዣ ሲነቃ ወጣቱ ሚኒስትር ፌድሮቭ ወደ መከላከያ ሚኒስትርነታቸው ይመለሳሉ ብሎ ተስፋ እንደሚያደርግም ገልጿል።

    ፕሬዚደንት ዜሌንስኪ በቅርቡ ባደረጉት ሹም ሽር ወጣቱ የመከላከያ ሚኒስትር ሚካኼሎ ፌድሮቭ ድጋሜ እንዳይሾሙ ያሳለፉት ውሳኔ በጦር ግንባር ባሉ ተዋጊዎች እና በቆሰሉት ጭምር ግራ መጋባትን እና ቁጣን አስከትሏል።

    ሐሙስ እለትም በኪየቭ ጎዳናዎች የተቃውሞ ሰልፍ ተካሂዷል።

    ለደኅንነቷ ሲባል ሜሪይና ስንል የምንጠራት ወታደር ውሳኔው ሁሉንም የጦሩን አባላት ያስደነገጠ ነው ብላለች።

    “ሳይናደዱ ይህንን በቃላት ለመግለጽ ያስቸግራል” ስትልም ስሜቷን አጋርታለች።

    ፕሬዝዳንት ዘሌንስኪ በዚህ ሳምንት ውሳኔያቸውን ሲያሳልፉ ሚካኼሎ ፌድሮቭ እና የጦሩ አዛዥ ጄኔራል ሲርስኪ ግልጽ ጠብ ውስጥ ገብተው ነበር።

    ሚኒስትር ፌድሮቭ፣ ጀኔራል ሲርስኪን ማሻሻያዎችን እንዳያደርጉ በማደናቀፍ ከስሰዋል።

    ዜሌንስኪም ፌድሮቭን በድጋሚ ለምን እንዳልሾሙ ሲያብራሩም፣ ሁለቱ ሰዎች በአንድ ክፍል ውስጥ መሆን አይችሉም ብለዋል።

    በ35 ዓመቱ ፌድሮቭ እና በሲርስኪ መካከል የ25 ዓመት የዕድሜ ልዩነት ያለ ሲሆን ግለሰቦቹ የተለያዩ የዩክሬን ገፅታዎችን የሚወክሉ ናቸው።

    ፌድሮቭ ጦርነቱን በዘመናዊ አስተሳሰብ እና ውስን ሃብቶችን በብቃት በመጠቀም በመምራት ባሳዩት ቁርጠነኝት ይወደሳሉ።

    የዩክሬን የጦር ኃይሎች ዋና አዛዥ የ60 ዓመቱ ጄኔራል ኦሌክሳንድር ሲርስኪም ከአራት ዓመታት በፊት ሩሲያ ሙሉ በሙሉ ወረራ ከከፈተች በኋላ ባሉት ሳምንታት ኪየቭን በተሳካ ሁኔታ በመከላከል እንደ ብሔራዊ ጀግና ይቆጠራሉ።

    ከዚያ በኋላ ግን የጀኔራሉ ስም ለሰው ልጅ ሕይወት ብዙም ዋጋ ከማይሰጥ ጊዜ ያለፈበት የውጊያ ስልት ጋር ተቆራኝቷል።

    "ፌድሮቭ አይፎን 16 ሲሆኑ ሲርስኪ ደግሞ የ1980ዎቹ ስልክ ማለት ናቸው” ሲሉ አንድ የጦር ተንታኝ እና የቀድሞ የደኅንነት መኮንን ኢቫን ስቱፓክን አመራሮቹ ያላቸውን ልዩነት ለቢቢሲ አስረድተዋል።

    "ሁለቱም ጠቀሜታቸው ተመሳሳይ ነው፤ ነገር ግን አገልግሎቱን የሚሰጡት በተለያየ መንገድ ነው" ብለዋል።

    የተቃውሞ ሰልፍ

    የፎቶው ባለመብት, Olga Ivashchenko/Bloomberg via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የመከላከያ ሚኒስትሩ ከሥልጣናቸው መነሳታቸውን ተከትሎ ሐሙስ እለት በኪየቭ ጎዳናዎች የተቃውሞ ሰልፍ ተካሂዷል
  5. ኡጋንዳ መኪና ተገልብጦ 20 ተማሪዎች ከሞቱ በኋላ ትምህርታዊ ጉዞን አገደች

    ከተገለበጠው አውቶብስ አጠገብ የቆሙ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, መኪናው በተገለበጠበት ወቅት ከትምህርታዊ ጉዞ የሚመለሱ ተማሪዎችን አሳፍሮ ነበር

    የኡጋንዳ መንግሥት ሐሙስ ዕለት በትምህርታዊ ጉዞ ላይ የነበሩ ተማሪዎችን ጭኖ የነበረ መኪና ተገልብጦ 20 ተማሪዎች እና አንድ አዋቂ ሰው ከሞቱ በኋላ ማንኛውንም ትምህርታዊ ጉዞ አገደ።

    በምሥራቃዊ ኢጋንዳ ካፕቾራዋ በደረሰው አደጋ የትምህርት ቤቱን ሠራተኞች ጨምሮ በርካቶች መጎዳታቸው ተገልጿል።

    የመጀመርያ ደረጃ የምርመራ ውጤት እንደሚያሳየው መኪናው ከአሽከርካሪው ቁጥጥር ውጪ ከመሆኑ በፊት የሜካኒካል ችግር አጋጥሞት ነበር።

    አደጋው የደረሰበት ሴክዋቲት የተባለው ኮረብታ በርካታ የመኪና አደጋ የሚደርስበት እንደሆነ የአካባቢው ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

    ኡጋንዳ በየዓመቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ የመኪና አደጋዎችን የምትመዘግብ ሲሆን ይህ ግን ሕጻናት ላይ የደረሰ እና በአገሪቱ ታሪክ ከፍተኛ ሆኖ የሚጠቀስ ነው።

    የትምህርት ሚኒስትሩ ጆን ችሪሶስቶም ሙዪንጎ በአደጋው ላይ የሚደረገው ምርመራ ሙሉ በሙሉ እስከሚጠናቀቅ ድረስ ማንኛውም ትምህርታዊ ጉዞ መታገዱን ባስታወቁበት ወቅት “እንደ አፋጣኝ የጥንቃቄ እርምጃ ለልጆቻችን ደኅንነት የሆነ ነገር ማድረግ አለብን” ብለዋል።

    “ሕዝባችን ትልቅ ነገር አጥቷል። ከአደጋው የተረፉት ተገቢው እንክብካቤ እንዲያገኙ እጅ ለእጅ ተያይዘን መሥራት ይኖርብናል” ሲሉ አክለዋል።

    የትራፊክ ፖሊስ ቃል አቀባይ ማይክል ካናኑራ ሐሙስ ዕለት የተከሰተውን አደጋ ሲገልጹ “አሽከርካሪው መኪናውን መቆጣጣር ባለመቻሉ ከመንገድ ወጥቶ ከቋጥኝ ጋር ተጋጭቶ ተገልብጧል” ብለዋል።

    አውቶብሱ ያሳፈራቸው በቺክዋቲት መንደር የሚገኘው የኪንግ ዴቪድ የመካከለኛ ደረጃ ተማሪዎችን ነበር።

    የአካባቢው አስተዳደሪ የሆኑት ባላም አቴኒዬ ባሩጋሃራ በኤክስ ገጻቸው ላይ “በሚያሳዝን ሁኔታ 20 ሕጻናት እና አንድ አዋቂ፤ የትምህርት ቤቱ መሥራች እና ዳይሬክተር የነበሩት ታዲዮ ስሴካዴ ወደ ፈጣሪያቸው ሄደዋል” ብለዋል።

  6. የአሜሪካ ጦር ለሰባት ተከታታይ ምሽት በኢራን ላይ ድብደባ መፈጸሙን አስታወቀ

    አርብ ዕለት የተጋሩ ምስሎች በሆርሞዝጋን የሚገኝ ድልድይ መመታቱን ያሳያሉ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, አርብ ዕለት የተጋሩ ምስሎች በሆርሞዝጋን የሚገኝ ድልድይ መመታቱን ያሳያሉ

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከቴህራን ጋር የተደረሰው የተኩስ አቁም “ማብቃቱን” ካስታወቁ በኋላ የአሜሪካ ጦር ለሰባተኛ ምሽት ድብደባ መፈጸሙን አስታወቀ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) በኤክስ ገጹ ላይ ባጋራው መግለጫ፣ ጦሩ “የቅኝት ጣቢያዎችን፣ የወታደራዊ ሎጂስቲክ መሠረተ ልማቶችን፣ ከምድር በታች የሚገኙ የጦር መሣሪያ ማከማቻዎችን እና የባሕር ኃይል አቅሟ” ላይ ድብደባ መፈጸሙን አስታውቋል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ በበኩሉ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ በተቀበሩ ፈንጂዎች ሁለት የነዳጅ ጫኝ መርከቦች መፈንዳታቸውን ገልጿል። ሴንትኮም ግን መረጃው ሐሰት ነው ሲል አስተባብሏል።

    የዮርዳኖስ ጦር ምሽቱን ከኢራን የተወነጨፉ አስር ሚሳዔሎችን ማክሸፉን እና ምንም ዓይነት ጉዳት አለማድረሳቸውን ገልጿል።

    ሴንትኮም ለበርካታ ሰዓታት ድብደባውን ከፈጸመ በኋላ ከእኩለ ለሌሊት በፊት ማቆሙን በመግለጫው ላይ አመልክቷል።

    ማዕከላዊ ዕዙ በመግለጫው ሌሊቱን ለፈጸማቸው ድብደባዎች “የአሜሪካ ጦር ተዋጊ ጄቶችን፣ ድሮኖችን እና የባሕር ኃይሉን ተጠቅሟል” ብሏል።

    ፋርስ የዜና ወኪል በበኩሉ ሁለት የነዳጅ ጫኝ መርከቦች “ፈንጂ በተቀበረበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ደቡባዊ ክፍል ሲያልፉ ፈንድተው በእሳት ተያይዘዋል” ብሎ የዘገበ ሲሆን ሴንትኮም በኤክስ ገጹ ላይ “ልክ እንደ ሌሎቹ የአብዮታዊ ዘቡ መረጃዎች ሁሉ ይህም ሐሰት ነው” ሲል አስተባብሏል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል እየተካሄደ ባለው ውጊያ የተነሳ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ቁጥር እጅጉን ቀንሷል።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ የዓለም አንድ አምስተኛ የነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፍበት መስመር ነው።

  7. ቴህራን፣ አሜሪካ የሰላማዊ ዜጎች መጠቀሚያ የሆኑ መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት አድርሳለች ስትል ከሰሰች

    ቢቢሲ ቬሪፋይ በሆርሞዝጋን ግዛት በሚገኝ ድልድይ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጧል

    የፎቶው ባለመብት, SocialMedia

    የምስሉ መግለጫ, ቢቢሲ ቬሪፋይ በሆርሞዝጋን ግዛት በሚገኝ ድልድይ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጧል

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የሚካሄደው የሰላም ድርድሩ ከተቋረጠ ወዲህ የአሜሪካ ጦር በቅርቡ በፈፀመው የአየር ጥቃት የሲቪል መሠረተ ልማቶችን እየደበደበ ነው ስትል ቴህራን ከሰሰች።

    የመንግሥት ሚዲያዎች እና የአካባቢ ባለሥልጣናት ድልድዮች፣ የባቡር ጣቢያ እና የአየር ማረፊያ መመታታቸውን ተናግረዋል። ቢቢሲ ቬሪፋይ በሆርሞዝጋን ግዛት በሚገኝ ድልድይ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጧል።

    የአሜሪካማዕከላዊ ዕዝ (ሴንቲኮም) የዒላማዎቹንዝርዝር ባይገልጽም፣ ጥቃቶቹ "የኢራንን ወታደራዊ አቅም የበለጠ ለማዳከም" የታለሙ ናቸውብሏል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቴህራን የካቲት 21 2018 ዓ.ም. በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃቶች የተጀመረውን ጦርነት ለማስቆም ኢራን ወደ ድርድር እንድትመለስ ለማስገደድ ድልድዮችን እና የኃይል ማመንጫ ጣቢያዎችን እንደሚመቱ ዝተው ነበር።

    ኢራን የአሜሪካ ጦር ጥቃትን ተከትሎ በባህረ ሰላጤው ውስጥ በሚገኙ የዩኤስኤ ጦር ሰፈሮች እና አጋሮች ላይ የበቀል እርምጃ እንድትወስድ አድርጓታል።

    አሜሪካ ለስድስት ተከታታይ ምሽቶች በኢራን ዒላማዎች ላይ የአየር ድብደባ ስትፈጽም ቆይታለች።

    የኢራን የመንግሥት ሚዲያዎች እና የአካባቢው ባለሥልጣናት ሐሙስ ምሽት ላይ በደቡብ ምሥራቅ ኢራን የሚገኘው የኢራንሻህር አውሮፕላን ማረፊያ፣ የባቡር ጣቢያ እና በሆርሞዝጋን ግዛት የሚገኙ ስድስት ድልድዮች ጥቃት እንደ ደረሰባቸው ዘግበዋል።

    በሆርሞዝጋን የሚገኙ የክልል ባለሥልጣናት ደግሞ ሰባትሰዎች መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል።

    ቢቢሲ ቬሪፋይ እና ቢቢሲ ፐርሺያ በጋሪቭህ ድልድይ ላይ የደረሰውን ጉዳት የሚያሳይ ቪዲዮን ትክክለኛለነት አረጋግጠዋል፤ በሌሊት የተቀረጹት ቪዲዮዎች በድልድዩ ላይ የእሳት ነበልባል ሲንቀለቀል አሳይተዋል።

    በቀን የተቀረጹ ምስሎች በተሰበረው ድልድይ ዙሪያ የመንገድ ፍርስራሽ ያሳያል።

    ሴንትኮም በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ ቢጠየቅም ቀደም ሲል ባወጣው መግለጫ ላይ የሚያክለው ምንም ነገር እንደሌለ ተናግሯል።

    ትራምፕ በሚያዝያ ወር አሜሪካ በኢራን ድልድዮችንና የኃይል ማመንጫዎችን ጨምሮ የሲቪል መሠረተ ልማቶችን እንደምትደበድብ ከተናገሩ በኋላ፣ የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ኃላፊ ቮልከር ቱርክ "ሆን ብሎ ሲቪሎችንና የሲቪል መሠረተ ልማቶችን ማጥቃት የጦር ወንጀል ነው" ብለዋል።

  8. ፊፋ ለዓለም ዋንጫ አሸናፊዎች ቀለበት ሊሸልም ነው፤ ትራምፕ የፍጻሜውን ውድድር ይታደማሉ

    ፊፋ የሚሸልመውን ቀለበት በድረ ገጹ ላይ ይፋ አድርጓል

    የፎቶው ባለመብት, Fifa.com

    የምስሉ መግለጫ, ፊፋ የሚሸልመውን ቀለበት በድረ ገጹ ላይ ይፋ አድርጓል

    ፊፋ እሁድ ዕለትበአርጀንቲና እና በስፔን መካከል በሚካሄደው የፍፃሜ ጨዋታ አሸናፊ ለሚሆነው ቡድን የዓለም ዋንጫ ቀለበቶችን እንደሚሸልም ሲገለጽ፣ ዶናልድ ትራምፕም ግጥሚያውን ይታደማሉ ተባለ።

    ለአሸናፊ ተጋጣሚዎች ቀለበቶችን መሸለም በአሜሪካ ስፖርት ውስጥ የተለመደ ባህል ነው።

    የዓለም ዋንጫ አሸናፊ ለሚሆነው ቡድን 30 ቀለበቶች የሚቀርቡ ሲሆን፣ በተጨማሪ 1,996 ቀለበቶች ለደጋፊዎች ይሸጣሉ። በእያንዳንዱ ቀለበት ላይ አነስተኛ የዓለም ዋንጫ እና ጽሑፍ ተቀርጾበታል።

    ዋንጫውን ለአሸናፊው ቡድን የሚያበረክቱት ፕሬዝዳንት ትራምፕ እስካሁን ድረስ ከ102ቱ የዓለም ዋንጫ ጨዋታዎች መካከል በአንዱም ላይ አልተገኙም።

    አሜሪካ በቤልጂየም ተረትታ ከመሰናበቷ በፊት ያደረገቻቸውን ጨዋታዎችንም ቢሆን አልተከታተሉም።

    በካናዳ የተከሰተውን ሰደድ እሳት ተከትሎ በኒው ዮርክ የሚኖረው አየር ሊበከል እንደሚችል ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷል።

    ነገር ግን በሜትላይፍ ስታዲየም የሚካሄደው የፍፃሜ ውድድር ላይ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር የሚጠቁም ምንም ነገርየለም።

    የፊፋ ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ ትራምፕ በፍፃሜው ጨዋታ ላይ እንደሚገኙ አስቀድመው ተናግረው ነበር፤ የዋይት ሐውስ የፕሬስ ሴክሬታሪ ካሮሊን ሌቪት ይህንኑ አረጋግጠዋል።

    አሜሪካ ከቦሲኒያ ሄርዜጎቪኒያ ጋር ባደረገችው የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ላይ በተቃራኒው ቡድን ላይ በሠራው ጥፋት ለአሜሪካው አጥቂ ፎላሪን ባልገን የተሰጠው ቀይ ካርድ እንዲታገድ መደረጉን ተከትሎ በፊፋ ፕሬዚዳንት ላይ ከፍተኛ ትችት ቀርቧል።

    የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማኅበር (ፊፋ) አጥቂው በቀጣዩ የአገሪቱ ብሔራዊ ቡድን ጨዋታ እንዳይሳተፍ የሚያግደው ውሳኔን የሻረው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በጉዳዩ ላይ ጣልቃ ከገቡ በኋላ ነው።

    በዓለም ዋንጫ ታሪክ 189 ጊዜ ቀይ ካርድ የተሰጠ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ ቀጣዩን ጨዋታ ያለመሳተፍ ዕገዳ ተፈጻሚ ያልሆነው የአሁኑን ጨምሮ በሁለት ተጫዋቾች ላይ ብቻ ነው።

    የዘንድሮው ዓለም ዋንጫ በአሜሪካ፣ በሜክሲኮ እና በካናዳ አስተናጋጅነት የተካሄደ ነው።

    ቅዳሜ ዕለት እንግሊዝ ከፈረንሳይ ለሦስተኝ ደረጃ የምትጫወት ሲሆን አርጀንቲና እና ስፔን ደግሞ እሁድ ዕለት ይጋጠማሉ።

  9. የዩኬ ፖሊስ ለኢራን ደኅንነት መሥሪያ ቤት ድጋፍ አድርጓል ያለውን ግለሰብ ከሰሰ

    የብሪታኒያ ፖሊስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የብሪታኒያ ፖሊስ አርብ ዕለት የኢራን የደኅንነት መሥሪያ ቤትን አግዟል ባለው የ39 ዓመት ግለሰብ ላይ ክስ መመሥረቱን አስታወቀ።

    ፖሊስ ቫሂድ አበሪ የተባለው የሊቨርፑል ነዋሪ በቁጥጥር ውሎ ማዕከላዊ እንግሊዝ ወደ ሚገኝ ፖሊስ ጣቢያ መወሰዱን እና በርሚንግሃም እና ሊቨርፑል የሚገኙ መኖሪያ ቤቶች ላይ ፍተሻ ማካሄዱን አስታውቋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) የደኅንነት ባለሥልጣናት በተደጋጋሚ ኢራን በአገሪቱ ውስጥ አለመረጋጋት ለመፍጠር ወንጀለኛ ቡድኖችን ልትጠቀም ትችላለች በማለት ሲያስጠነቅቁ ነበር።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ ጊዜ ጀምሮ በብሪታኒያ በርካታ ፀረ ሴማዊ ጥቃቶች ተፈጽመዋል።

    በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ብሪታኒያ በኢራን መንግሥት የሚደገፉ አለመረጋጋቶችን ለማስቀረት በሚል ለኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የሚደረግ ድጋፍን አግዳለች።

    አበሪ እስካሁን ድረስ ለየትኛውም ማኅበረሰብ ወይንም ግለሰብ ስጋት መሆኑ አልተለየም ተብሏል።

    ነገር ግን በውጭ የደኅንነት ተቋማት የሚደረጉ ጣልቃ ገብነቶችን ለመከላከል በፍጥነት መንቀሳቀስ እንዳለባቸው ተናግረዋል።

    ባለፈው ሳምንት ብሪታኒያ የኢራን ከፍተኛ ዲፕሎማትን ጠርታ ሁለት ሮማኒያውያን ስለተከሰሱበት በለንደን ስለተፈጸመ የስለት ጥቃት አነጋግራቸዋልች።

    በለንደን የሚገኘው የኢራን ኤምባሲ ከዚህ ቀደም እንዲህ ዓይነቱን ክስ “መሠረት የሌለው፣ ፖለቲካዊ እና ጠብ አጫሪ ውንጀላ ነው” ሲል ውድቅ አድርጎት ነበር።

    በቁጥጥር ስር የዋለው ግለሰብ አርብ ከሰዓት በለንደን በሚገኝ ፍርድ ቤት ይቀርባል ተብሎ ይጠበቃል።

  10. በጋና ፕሬዝዳንት ላይ ሐሰተኛ ዜና ያሠራጨችው ቲክቶከር ተፈረደባት

    ጋናዊቷ ቲክቶከር ካሚላ አልሃሳን

    የፎቶው ባለመብት, Camilla Alhassan/TikTok

    የምስሉ መግለጫ, ጋናዊቷ ቲክቶከር ካሚላ አልሃሳን

    ጋናዊቷ ቲክቶከር ስለ አገሪቱ ፕሬዝዳንት ጆን ማሃማ ባጋራቻቸው ሐሰተኛ ዜናዎች የተነሳ ጥፋተኛ መሆኗ በመረጋገጡ የአንድ ዓመት እስር ተፈረደባት።

    በግንቦት እና ሰኔ ወር መጀመሪያ ላይ ቲክቶከሯ ካሚላ አልሃሳን ፕሬዝዳንቱ የአውሮፓውያኑ 2024ቱን አጠቃላይ ምርጫ እንዲያሸንፉ ለአምልኮ ሥርዓት ማስፈጸሚያ 32 ላሞችን መስዋዕት እንዳደረጉ የሚገልጹ ተከታታይ ቪዲዮዎችን አጋርታለች።

    የ43 ዓመቷ ቲክቶከር በተጨማሪም መንግሥት በቅርቡ በጎርፍ ለተጎዱ ሰዎች የንፅህና መጠበቂያዎችን ለማከፋፈል የወሰደው እርምጃ ፈጽመውታል ያለችውን አምልኮ ሥርዓት ለመደበቅ የተደረገ ሙከራ ነው ስትል ተናግራለች።

    ጉዳዩን የተመለከቱት ዳኛ ቀላል ቅጣት እንዲጣል የቀረበውን ይግባኝ ውድቅ በማድረግ ተመሳሳይ ድርጊትን ያስቀራል ያሉትን የእስር ቅጣት ወስነዋል።

    ዐቃቤ ሕግ በቲክቶክ ላይ ከ70 ሺህ በላይ ተከታዮች ያሏት አልሃሳን በፕሬዝዳንቱ ላይ ተከታታይ የሐሰት እና የስም ማጥፋት ውንጀላዎችን አቅርባለች ሲል ተከራክሯል።

    በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ አልሃሳን እንድትታሰር ምክንያት የሆኑት በስፋት የተጋሩት ቪዲዮዎቿ በጋና በማኅበራዊ ሚዲያ ስለሚሠራጩ ሐሰተኛ መረጃዎች የተነሳ በወንጀል እና ሀሳብን በነፃነት የመግለጽ ነፃነት መካከል ያለውን ሚዛን እንዴት መጠበቅ እንደሚቻል ክርክር አስነስተዋል።

    ዳኛው ፍርዱ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የሐሰተኛ መረጃ ሥርጭት ለመግታት አስፈላጊ ነበር ብለዋል።

    በጋና ተፅዕኖ ፈጣሪ ሲታሰር ይህ የመጀመሪያው አይደለም።

    በመስከረም ወር፣ ክዋሜ ንክሩማህ II በመባል የሚታወቀው ታዋቂው ቲክቶከር ዴቪድ ክዎድዎ ፕራህ አፍፉል የግድያ ዛቻ በመፈጸም እና ሰላምን የሚያደፈርስ አጸያፊ ተግባር በመፈጸም ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ በኋላ የሰባት ወራት እስራት ተፈርዶበታል።

    ቲክቶከሩ በስፋት በተጋራው ቪዲዮው ላይ ፕሬዝዳንት ማሃማን እና የፓርላማ አባላትን እንደሚገድል አስፈራርቶ ነበር።

    ባለፈው ዓመት ፕሬዝዳንቱ መንግሥታቸው የማኅበራዊ ሚዲያዎችን "ለማጽዳት" መንገዶችን እያሰበ መሆኑን ተናግረዋል። የአገሪቱ ባለሥልጣናትም የተሳሳተ እና የተዛባ መረጃ የሚያሠራጩትን ተከታትለው እንዲያስሩ መመሪያ ሰጥተዋል።

    “ለጋናውያን ሐሰተኛ ወሬዎችን፣ የጥላቻ ንግግሮችን የምታሠራጩ እና ፍርሃትና ድንጋጤ የሚፈጥሩ ድርጊቶችን የምትፈጽሙ ከሆነ እናገኛችኋለን’ የሚል ምልክት እያስተላለፍኩ ነው” ሲሉ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተናግረዋል።

  11. ኩዌት በኢራን ጥቃት የውሃ ማጣሪያ እና የኃይል ማመንጫ እንደተመታባት ገለጸች

    የኢራን ሚሳዔል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኩዌት፤ የኢራን ጦር በፈጸማቸው ጥቃቶች የጨው ውሃ ማጣሪያ እና የኃይል ማመንጫ ጣቢያ ላይ ጉዳት መድረሱን አስታወቀች።

    ካለፈው ሳምንት አንስቶ ያገረሸው የአሜሪካ እና ኢራን ግጭት፤ ትናንት ምሽትም ቀጥሎ ታይቷል። አሜሪካ በኢራን የተለያዩ ሥፍራዎች ካደረሰችው ጥቃት በኋላ ቴህራን በምላሹ ጎረቤቶቿ የሆኑ የቀጣናው አገራትን ዒላማ አድርጋለች።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጥቃት ከሰነዘረባቸው አገራት አንዷ ኩዌት እንደሆነች ገልጾ ነበር። የኩዌት የኤሌክትሪክ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ የኢራን ጥቃት በኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ እና የጨው ውሃ ማጣሪያ ላይ ጉዳት ማድረሱን አስታውቋል።

    ጥቃቱ በሥፍራዎቹ “ቃጠሎ እንዲነሳ፣ ጉዳት እንዲሰርስ እና በርካታ የማምረቻ ክፍሎች ከአገልግሎት ውጪ እንዲሆኑ አድርጓል” ብሏል።

    በተቋማቱ ላይ ስለደረሰው ጉዳት ተጨማሪ መረጃ አልተገለጸም።

    ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ዜጎች “በዚህ የተለየ ወቅት የኤሌክትሪክ ፍጆታቸውን እንዲያስተካክሉ እና ኤሌክትሪክ እንዲቆጥቡ” ጠይቋል።

  12. የዋይት ሀውስ የጽሑፍ ማንበቢያ ማሽን ተቆጣጣሪ የትራምፕ ንግግር ላይ ተወራርዶ 100 ሺህ ዶላር በማግኘት ተከሰሰ

    የዋይት ሀውስ የንግግር ጽሑፍ ማንበቢያ ማሽን (ቴሌፕሮምፕተር) ኦፕሬተር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የዋይት ሀውስ የንግግር ጽሑፍ ማንበቢያ ማሽን (ቴሌፕሮምፕተር) ኦፕሬተር፤ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ንግግሮች ላይ ውርርድ በማድረግ 100,000 ዶላር ገደማ አግኝቷል በሚል ምርመራ ተከፈተበት።

    ቴሌፕሮምፕተር በጽሑፍ የተዘጋጀ ንግግርን በስክሪን ላይ የሚያሳይ ማሽን ነው። እንደ ፕሬዝዳንቶች ያሉ ባለሥልጣናት ወረቀት ሳይዙ ስክሪኑን በመመልከት ንግግራቸውን ለታዳሚዎች እንዲያቀርቡ ያስችላል።

    ከአውሮፓውያኑ 2016 አንስቶ የዋይት ሀውስ ሠራተኛ የሆነው ገብርኤል ፔሬዝ፣ በአሜሪካው ቤተ መንግሥት የሚገኘው እና ፕሬዝዳንቱን ጨምሮ የተለያዩ ባለሥልጣናት ለንግግራቸው የሚጠቀሙበት ቴሌፕሮምፕተር ተቆጣጣሪ ነው።

    ፔሬዝ፣ ፕሬዝዳንቱ በሚያደርጓቸው ዋና ዋና ሕዝባዊ ንግግሮች የሚጠቀሟቸው ቃላት ላይ ሲወራረድ ነበር የሚል ክስ ቀርቦበታል።

    ውርርዱን ሲያካሂድ የነበረው ‘ካልሺ’ በተባለው እና ሰዎች በዓለም የሚከናወኑ ኹነቶችን በተመለከተ በመገመት መወራረድ በሚያስችለው ድረ ገጽ ላይ ነው። ኩባንያው ይህንን ድርጊት በተመለከተ ለተቆጣጣሪው መሥሪያ ቤት ማሳወቁን አረጋግጧል።

    ካልሺ የዋይት ሀውሱ ሠራተኛ ያገኘውን ትርፍ ከማውጣቱ በፊት መወራረጃ አካውንቱ እንዲታገድ ማድረጉን በሪፖርቱ ገልጿል።

    ኩባንያው የሠራተኛውን እንቅስቃሴ መከታተል የጀመረው ባለፈው መጋቢት ላይ ያልተለመደ ዓይነት ውርርድ ከተመለከተ በኋላ መሆኑን ለቢቢሲ ገልጿል።

    ይህ ዓይነት እንቅስቃሴ የተስተዋለው የተለያዩ አካላት በሚያደርጓቸው ንግግሮች የሚጠቀሟቸውን ቃላት በመገመት እንዲወራረዱ በሚያስችለው የግብይት ዓይነት ላይ ነው።

    በዚህ መልኩ ውርርድ የሚያደርጉ ተጫዋቾች፤ በንግግሮች ውስጥ የሆነ አገር፣ ኢኮኖሚያዊ ቃል ወይም የቅስቀሳ መፈክር ይጠቀስ እንደሆነ በመገመት ገንዘብ ያስይዛሉ።

    ካልሺ “እንደ ፕሬዝዳንቶች እና የብሔራዊ ባንክ ገዢዎች ያሉ የፖለቲካ መሪዎች ቃላት በፎሬክስ፣ የነዳጅ ኦፕሽን እና የአክስዮን ገበያ ላይ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር እንዲንቀሳቀሱ ያደርጋሉ” በማለት አስረድቷል።

    ካልሺ ተወራራጁ በዋይት ሀውስ ውስጥ በጽሑፍ የተዘጋጁ ንግግሮች ወደ ማንበቢያው ማሽን (ቴሌፕሮፕተር) የሚያስገባ የፌደራል ሠራተኛ መሆኑን የደረሰበት የአካውንቱን መረጃ በመጠቀም ነው።

    የዋይት ሀውስ ሠራተኛው ያገኘውን 90 ሺህ ዶላር ከማውጣቱ በፊት ታግዶበታል።

    የዋይት ሀውስ ፕሬስ ሴክሬታሪያት ካሮሊን ሌቪት፣ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ስለ ቴሌፕሮምፕተር ኦፕሬተሩ ጉዳይ እንደሚያውቁ ተናግረዋል። በአሁኑ ሰዓት ሠራተኛው ያለ ክፍያ እረፍት እንዲወጣ መደረጉን የገለጹት ቃል አቀባይዋ፤ ከአሁን በኋላም በዋይት ሀውስ መሥራት እንደማይቀጥል አስታውቀዋል።

  13. በኡጋንዳ የተማሪዎች አውቶብስ ተገልብጦ ቢያንስ 20 ልጆች ሞቱ

    በትምህርታዊ ጉዞ ላይ የነበሩ ተማሪዎችን ጭኖ ሲጓዝ የነበረ አውቶብስ በምሥራቃዊ የአገሪቱ ክፍል ተገልብጧል

    የፎቶው ባለመብት, Uganda Police Force/X

    በኡጋንዳ በደረሰ የትራፊክ አደጋ ቢያንስ 20 ልጆች እና አንድ አዋቂ ሰው መሞታቸው ተገለጸ።

    በትምህርታዊ ጉዞ ላይ የነበሩ ተማሪዎችን ጭኖ የተጓዘው አውቶብስ በምሥራቃዊ የአገሪቱ ክፍል የተገለበጠ ሲሆን፤ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ልጆች ላይ ከደረሱ የተሽከርካሪ አደጋዎች የከፋው ነው ተብሏል።

    የትምህርት ቤት ሠራተኞችን ጨምሮ ሌሎች በርካታ ሰዎችም በአደጋው ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    አደጋው የተከሰተው ትናንት ሐሙስ ማታ ካምቾርዋ በተባለ አካባቢ ነው።

    የመጀመሪያ ደረጃ የምርመራ ውጤት እንደሚያሳየው ለአደጋው መንስዔ አውቶብሱ የገጠመው የቴክኒክ ብልሽት ሲሆን፤ መኪናው ከአሽከርካሪው ቁጥጥር ውጭ ሆኗል።

    አደጋው የደረሰበት አካባቢ ከዚህ ቀደምም የትራፊክ አደጋዎች የተከሰቱበት እንደሆነ ተገልጿል።

    ፖሊስ ባወጣው መግለጫ “አሽከርካሪው መኪናውን መቆጣጠር እንዳልቻለ ሪፖርት ተደርጓል። መኪናው መንገድ ስቶ ከግዙፍ ድንጋይ ጋር ተጋጭቶም ተገልብጧል” ብሏል።

    የአካባቢው የመንግሥት ባለሥልጣን “በሚያሳዝን ሁኔታ 20 ልጆች እና አንድ አዋቂ ወደ ፈጣሪ ሄደዋል” በማለት በኤክስ ገጻቸው ሐዘናቸውን ገልጸዋል።

  14. ኢራን በኦማን፣ ኩዌት፣ ባሕሬን እና ሶሪያ ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን መምቷን አስታወቀች

    የኢራን ባንዲራን የያዙ ሰልፈኞች የቀድሞ ጠቅላይ መሪ አሊ ኻሜኒ ምስል ከሚታይበት ትልቅ ቢልቦርድ ስር ቆመው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ኦማን ውስጥ የሚገኝ የአሜሪካ የባሕር ኃይል መከታተያ ራዳር ሥፍራዎችን እንዲሁም ኩዌት እና ባሕሬን ውስጥ የሚገኙ ዒላማዎችን መምታቱን አስታወቀ። ሶርያ ውስጥ የሚገኝ የአሜሪካ የልዩ ዘመቻ ዕዝ ማዕከል ላይም ጥቃት መፈጸሙን ገልጿል።

    ኦማን ውስጥ በተፈጸመው ጥቃት “የባሕር ኃይል የቁጥጥር ራዳር እና የአሜሪካ አየር መቆጣጠሪያ ራዳር” መመታታቸውን ዘቡ ባወጣው መግለጫ ጠቅሷል።

    “በኃይል የሚፈጸሙ የአጸፋ ዘመቻዎች ይቀጥላሉ። የሆርሙዝ ወሽመጥም በአብዮታዊ ዘቡ ባሕር ኃይል ቁጥጥር ሥር እንደሆነ ቀጥሏል” ብሏል።

    የአሜሪካ የልዩ ዘመቻ ዕዝ ማዕከል ላይ ተፈጽሟል በተባለው የሶርያው ጥቃት፤ “የራዳር ሥርዓት፣ በርካታ የልዩ ሄሊኮፕተሮች እና በርከት ያሉ አሜሪካውያን ኃይሎች” ዒላማ መደረጋቸውን ጠቅሷል።

    እንደ አብዮታዊ ዘቡ ገለጻ፤ በዮርዳኖስ ድንበር አቅራቢያ በሚገኘው አል ታንፍ የተፈጸመው ድንገተኛ ጥቃት፤ ከሁለት ቀናት በፊት በኢራናውያን ወታደሮች ላይ ለተፈጸመው ግድያ የአጸፋ እርምጃ ነው።

    ሶርያም ሆኑ አሜሪካ እስካሁን ተፈጸመ ስለተባለው ጥቃት አስተያየት አልሰጡም።

    የዮርዳኖስ ጦር ግን ወደ አገሪቱ የተወነጨፉ ሦስት የኢራን ሚሳዔሎችን ጉዳት ወይም ውድመት ሳይደርስ መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    ኢራን አብዮታዊ ዘብ አዲሱን ጥቃት ከመፈጸሙ አስቀድሞ አሜሪካ “በርካታ የኢራን ጦር ዒላማዎችን” መምታቷን ገልጻለች።

    ኢራን በበኩሏ ድልድዮች፣ ባቡር ጣቢያ እና የአየር ማረፊያን ጨምሮ በተለያዩ የሲቪል መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት እንደተፈጸመባት አስታውቃለች።

    ሁለቱም አገራት የሚፈጽሟቸው ጥቃቶች እየተባባሱ ባሉበት በዚህ ወቅት፤ ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ ሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን እንደተዘጋ ነው።

  15. አሜሪካ ለስድስተኛ ተከታታይ ምሽት በከፈተችው ጥቃት የኢራን የሲቪል መሠረተ ልማቶች መደብደባቸው ተገለጸ

    ጥቃት ደረሰበት ኢራን ድልድይ

    የፎቶው ባለመብት, irib

    የምስሉ መግለጫ, ቢቢሲ በሆርሞዝጋን ግዛት ድልድይ መመታቱን አረጋግጧል

    አሜሪካ እና ኢራን ሆርሙዝ ወሽመጥን ለመቆጣጠር የሚደርጉት ውጊያ ቀጥሎ፤ የዋሽንተግን ጦር ለስድስተኛ ተከታታይ ምሽት በኢራን አዲስ ዙር ጥቃት ፈጸመ።

    ሐሙስ ሌሊት የደረሱት ጥቃቶች በድጋሚ ያገረሸው የሁለቱ አገራት ግጭት እየተባባሰ መሆኑን የሚያመለክቱ ናቸው።

    አሜሪካ የኢራን ድልድዮች፣ ባቡር ጣቢያ እና የአየር ማረፊያን ጨምሮ በተለያዩ የሲቪል መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት መፈጸሟን የቴህራን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል። በሆርሞዝጋን ግዛት ከባንደር አባስ በምዕራብ አቅጣጫ የሚገኝ አንድ ድልድይ መመታቱን ቢቢሲ አረጋግጧል።

    ቢቢሲ ስለ ጥቃቱ ለዋይት ሀውስ እና ለአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ጥያቄ አቅርቧል።

    በተጨማሪም የአሜሪካ ሚሳዔሎች በሆርሙዝ አቅራቢያ የሚገኘውን ቃሽም ደሴት እንዲሁም የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ መገኛ የሆነው ቡሼህርን መትተዋል። የወደብ ከተማው ባንዳር አባስም የሚሳዔል ዒላማ ሆኗል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ የተፈጸሙት ጥቃቶች "የኢራንን ወታደራዊ አቅም ይበልጥ ለማዳከም" ያለሙ እንደሆኑ ገልጿል። በተጨማሪም አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የጣለችውን እገዳ ሊጥስ የነበረ አንድ መርከብን መቆጣጠሩን አስታውቋል።

    ሴንትኮም በዚህ ዙር ጥቃት የተደበደቡ በሚል በዘረዘራቸው “በርካታ የኢራን ጦር ዒላማዎች” ውስጥ ድልድዮችን አልጠቀሰም።

    በዚህ ጥቃት የተሳተፉት የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች፣ ድሮኖች እና የጦር መርከቦች የኢራንን "የባሕር ዳርቻ መከታተያ እና የአየር መከላከያ ጣቢያዎችን፣ ወታደራዊ የሎጂስቲክስ መሠረተ ልማት እና የባሕር ኃይል አቅሞችን" መምታታቸውን ገልጿል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ቴህራን ወደ ድርድር የማትመለስ ከሆነ በአገሪቱ ውስጥ የሚገኙ ድልድዮች እና የኃይል ማመንጫዎችን እንደሚመቱ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ዝተው ነበር።

    ፕሬዝዳንቱ ባለፈው ሚያዝያ ላይም ድልድዮች እና የኃይል ማመንጫዎችን ጨምሮ የኢራን የሲቪል መሠረተ ልማቶች እንደሚደበድቡ መናገራቸው ይታወሳል።

    በወቅቱም የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ቮልከር ቱርክ፤ "ሆነ ብሎ ሲቪሎች እና የሲቪል መሠረተ ልማቶችን ማጥቃት የጦር ወንጀል" እንደሆነ መገናራቸው ይታወሳል።

    በ1949 የወጣው እና በጦርነት ወቅት የሚከበሩ ሰብአዊ ሥነ ምግባሮችን የሚዘረዝረው የጄኔቫ ስምምነት፤ ለሲቪሎች አስፈላጊ እንደሆኑ በሚታሰቡ ሥፍራዎች ላይ ጥቃት መፈጸምን ይከለክላል።

  16. የየመን ሁቲዎች የሳዑዲ አረቢያን የነዳጅ ማምረቻ ተቋማት እንደሚያጠቁ አስጠነቀቁ

    በሰነዓ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ የታየ ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በሰነዓ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ የታየ ጭስ

    ሁቲዎች ከሳዑዲ አረቢያ ጋር የሚያካሂዱት ግጭት የሚባባስ ከሆነ የሳዑዲን የነዳጅ ተቋማት እና ሌሎች ወሳኝ ተቋማት ዒላማ እንደሚያደርጉ አስጠነቀቁ።

    የሁቲ ታጣቂ ቡድን መሪ የሆነው አብዱል-ማሊክ ሁቲ እንደተናገረው "ሳዑዲ አረቢያ በአገራችን ላይ መጠነ ሰፊ ጥቃት በመክፈት ግጭቱን የምታባብስ ከሆነ፣ ሁሉም የነዳጅ ማምረቻ ተቋማቷ እና ወሳኝ ማዕከላቷ የሚሳዔሎቻችን እና የድሮኖቻችን ዒላማ ይሆናሉ” በማለት አስጠንቅቋል።

    ሰኞ ዕለት ሳዑዲ በሰነዓ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ ጥቃት ፈጽማለች በማለት ሁቲዎች የከሰሱ ሲሆን በምላሹም በሳዑዲ ውስጥ የሚገኝን ዒላማ ማድረጋቸውን አሳውቀዋል። በሁለቱ ወገኖች መካከል አሁን እየተካሄደ ያለው የተኩስ ልውውጥ በአውሮፓውያኑ 2022 ከተደረሰው ተኩስ አቁም ወዲህ በመካከላቸው ያለው ውጥረት መባባሱን ያሳያል።

    ሳዑዲ ተጨማሪ ጥቃት በሰነዓ ላይ የምትፈጽም ከሆነ ሪያድ የሚገኘው አውሮፕላን ማረፊያዋ ዒላማ እንደሚሆን የሁቲ ታጣቂ ቡድን መሪ ማስጠንቀቁን ኤኤፍፒ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    በሳዑዲ የሚደገፈው እና ኤደን ከተማ ውስጥ መቀመጫውን ያደረገው የየመን መንግሥት በሰነዓ ላይ የተፈጸመው ጥቃት የሁቲዎች አጋር የሆነችው የኢራን አውሮፕላን እንዳያርፍ ለማድረግ ነው ብሏል።

    ወደ የመን የአየር ክልል የሚገቡ አውሮፕላኖች የቅድሚያ ፈቃድ በሳዑዲ ከሚመራው የአካባቢው አገራት ጥምረት ማግኘት እንዳለበት የሚያስገድደው አሠራር ከአስር ዓመታት በላይ በሥራ ላይ ቆይቷል።

    የየመን መንግሥት እና ደጋፊዎቹ እንደሚሉት ይህንን የበረራ ፍቃድ ሁቲዎች እና ኢራን ከግዛቷ ቀጥታ በረራ በማድረግ ጥሰት እየፈጸሙ ናቸው ሲሉ ይከስሳሉ።

    ማክሰኞ ዕለት ሁቲዎች በሳዑዲ የሚመራው ጥምረት ያሰማራው የቅኝት ድሮንን መትተው መታላቸውን አሳውቀዋል።

  17. አሜሪካ የኃይል ተቋማቷን ካጠቃች ሁቲዎች የቀይ ባሕር የነዳጅ መተላለፊያን ለመዝጋት እንዲዘጋጁ ኢራን ማሳሰቧ ተዘገበ

    የሁቲ አማጺያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ የኢራን የኃይል ማመንጫ መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት የምትሰነዝር ከሆነ፤ የየመን ሁቲ አማጺያን በቀይ ባሕር የሚገኙ የነዳጅ መተላለፊያን ለመዝጋት እንዲዘጋጁ ቴህራን ማሳሰቧን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    የኢራን አመራሮች በጉዳዩ ላይ እንደተወያዩ እና በየመን አጋሮቻቸው ለሆኑት ሁቲዎች መልዕክቱ እንደተላለፈ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ሁለት ከፍተኛ የቴህራን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

    የሮይተርስ ዘገባ እንደሚጠቁመው ጉዳዩ ስሱ ከመሆኑ የተነሳ ባለሥልጣናቱ ማንነታቸው እንዲገለጽ አልፈቀዱም።

    ከዚህ ቀደም ስለ ጉዳዩ ምንም ያልተሰማ ሲሆን የሁቲ አማጺያንም በቅርቡ መልዕክቱ እንደደረሳቸው ተጠቁሟል።

    መልዕክቱ በምን መንገድ እንደተላለፈ እንዲሁም መልዕክቱ የተላለፈው ማክሰኞ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን የኃይል አቅርቦች መሠረተ ልማቶች ለመምታት ከዛቱ በኋላ ስለመሆኑ የሮይተርስ ምንጮች ማብራሪያ አልሰጡም።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና የሁቲ ቃል አቀባይ በጉዳዩ ላይ ከሮይተርስ አስተያየት እንዲሰጡ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ አልሰጡም።

  18. በአልጄሪያ በሕጻናት ማሳደጊያ ላይ በተነሳ እሳት ቢያንስ 11 ሰዎች ሞቱ

    የእሳት አደጋ ሠራተኞች ቃጠሎውን ለማጥፋት ጥረት ሲያደርጉ

    የፎቶው ባለመብት, Algeria's General Directorate for Civil Protection

    የምስሉ መግለጫ, የእሳት አደጋ ሠራተኞች ቃጠሎውን ለማጥፋት ጥረት ሲያደርጉ

    በሰሜን አፍሪካዊቷ አገር አልጄሪያ ውስጥ በሚገኝ ወላጆቻቸውን ያጡ ማሳደጊያ ላይ በተከሰተ የእሳት አደጋ ቢያንስ 11 ሰዎች ሕይወታቸው ሲያልፍ ሌሎች 19 ደግሞ ጉዳት ደረሰባቸው።

    በዋና ከተማዋ አልጀርስ ዳርቻ ላይ በምትገኘው ሚሐመድያ ተብላ በምትጠራ አካባቢ ባለው የእጓለሙታን ማዕከል ውስጥ የተነሳውን እሳት ለመቆጣጠር የእሳት አደጋ እና የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ጥረት እያደረጉ መሆናቸው ተዘግቧል።

    ባለ ሁለት ፎቅ በሆነው ሕንጻ ላይ ረቡዕ ሌሊት በተከሰተው የእሳት ቃጠሎ ጉዳት የደረሰባቸው ሕጻናት ማንነት እና ዕድሜ ይፋ አልተደረገም።

    በማሳደጊያው ውስጥ የነበሩ የአካል ጉዳት የነበረባቸው አምስት ሕጻናትን ማትረፍ መቻሉን የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች የገለጹ ሲሆን፣ የእሳቱ ምክንያት ምን እንደሆነ አልታወቀም።

    አደጋውን ተከትሎ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሲፊ ጋሪብ ጉዳት የደረሰባቸውን ሆስፒታል ተገኝተው ጎብኝተዋል።

    በአልጄሪያ በአሁኑ ጊዜ ከፍተኛ ሙቀት የተከሰተ ሲሆን በአገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል ውስጥ በርካታ ሰደድ እሳቶች እንዲከሰቱ ምክንያት ሆኗል።

  19. የአርጀንቲናውያን የዓለም ዋንጫ ፖለቲካዊ መልዕክት እና የሚጠበቀው የፊፋ ቅጣት

    የአርጀንቲና ተጫዋቾች ያሳዩት ምልዕክት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አርጀንቲና ተጫዋቾቿ የእንግሊዝን ብሔራዊ ቡድንን በዓለም ዋንጫ የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ካሸነፉ በኋላ፤ አገራቸው በፎክላንድ ደሴቶች ላይ ያላትን የይገባኛል ጥያቄ የሚደግፍ ጽሁፍ አሳይተዋል። ይህ ድርጊታቸው ከፊፋ የሥነ ምግባር ጥሰት ቅጣት እንደሚያስወስድ እየተጠበቀ ነው።

    የአርጀንቲና ቡድን አትላንታ ውስጥ በተካሄደው ጨዋታ እንግሊዝን 2 ለ 1 በሆነ ውጤት ያሸነፈ ሲሆን እሁድ በሚደረገው የፍፃሜ ጨዋታ ከስፔን ጋር ይገጥማል።

    የጨዋታው የመጨረሻ ፊሽካ ከተሰማ በኋላ የአርጀንቲና ተጫዋቾች 'ላስ ማልቪናስ' በሚል በማለት የሚጠሯቸው ደሴቶች የአገራቸው ግዛት መሆናቸውን የሚገልጽ ባነር ይዘው ታይተዋል።

    ደስታቸውን ሲገልጹ የያዙት ባነር "ፎልክላንድ ደሴቶች የአርጀንቲና ናቸው" የሚል ነው።

    የፎልክላንድ ደሴቶች፣ በደቡብ ምዕራብ አትላንቲክ ውቅያኖስ ላይ የሚገኙ የእንግሊዝ የባሕር ማዶ ግዛት አካል ሲሆኑ፣ በብሪታንያ እና በአርጀንቲና መካከል የሉዓላዊነት ይገባኛል ውዝግብ ርዕሰ ጉዳይ ሆነው ቀጥለዋል።

    ሁለቱ አገራት ከአውሮፓውያኑ ሚያዝያ እስከ ሰኔ 1982 ድረስ በአርጀንቲና ምሥራቃዊ የባሕር ዳርቻ 300 ማይል ርቀት በሚገኙት ደሴቶች ላይ ጦርነት አካሂደው ነበር።

    ለ74 ቀናት በዘለቀው ጦርነት 655 የአርጀንቲና ወታደሮች እና 255 የእንግሊዝ ወታደሮችን ሲሞቱ ከደሴቶቹ የመጡ ሦስት ሰዎችም በጦርነቱ ተገድለዋል።

    በአውሮፓውያኑ 2014 የአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ከስሎቬንያ ጋር ባደረገው የወዳጅነት ጨዋታ ተጫዋቾቹ ተመሳሳይ መልዕክት የያዘ ባነር በማሳየታቸው ፊፋ በአገሪቱ እግር ኳስ ማኅበር ላይ የ20 ሺህ ፓውንድ ቅጣት ጥሎበት ነበር።

    የዓለም እግር ኳስ የበላይ አስተዳዳሪ አካል የሆነው ፊፋ ይህ የአርጀንቲና ቡድን ድርጊት የተቋሙን የሚጥስ ነው ስላለ፤ ክስተቱን መርምሮ ቅጣት እንደሚያስተላለፍ እየተጠበቀ ነው።

  20. ኢራን በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን አጠቃች

    የኢራን ጦር

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን በከፈተችው አዲስ ዙር ጥቃት በጎረቤቶቿ የባሕረ ሰላጤው አገራት ውስጥ የሚገኙ አሜሪካ የጦር ሠፈሮችን መታች።

    ዮርዳኖስ፣ ኩዌት እና ባሕሬንን ጨምሮ በቀጣናው የሚገኙ ዒላማዎች ጥቃት እንደተፈጸመቸባው ኢራን ገልጻለች። የኢራን ጦር ሌሊት ላይ በፈጸመው ጥቃት ዮርዳኖስ ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ሠራዊት “የግንኙነት ሥርዓቶች እና የነዳጅ ማጠራቀሚያዎችን” መምታቱን እንዳስታወቀ ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ዮርዳኖስ ውስጥ ዒላማ ከተደረጉት ስፍራዎች አንዱ ‘አል አዝራቅ’ ጦር ሠፈር እንደሆነ የገለጸው ጦሩ፤ ቦታው “ፀረ ሚሳዔል መከላከያ ሥርዓት የሚገኝበት” እንደሆነ ጠቅሷል።

    ኩዌት ውስጥ በሚገኘው አሊ ሳሌም የጦር ሠፈር ደግሞ “የቅድመ ማስጠንቂያ ራዳር ሥርዓት” ዒላማ መደረጉን የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ገልጿል።

    አብዮታዊ ዘቡ እንደሚናገረው “የአሜሪካ ወታደሮች ኩዌት ውስጥ የሚሰበሰቡበት” ስፍራ ላይም ጥቃት ደርሷል። ጥቃቱ የተፈጸመው “ሚሳዔል እና ድሮን” በመጠቀም እንደሆነ አስታውቋል።

    በተመሳሳይ አሜሪካ ረቡዕ ሌሊት በመላው ኢራን በርካታ ስፍራዎች ላይ ጥቃት ፈጽማለች። ለስድስት ሰዓታት ቆየው ጥቃት ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ “ንጹኃን ባሕርተኞችን ስጋት ላይ ለመጣል ያላትን አቅም ያዳከመ” እንደሆነ የአሜሪካ ጦር ገልጿል።