የኢራን ጠቅላይ መሪ ሚስት ቀብር የባለቤታቸው አስከሬን ባልተገኘበት ተፈጸመ
በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃት ከወራት በፊት የተገደሉት የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ ባለቤት ዛሃራ ሃዳድ የቀብር ሥነ ሥርዓት ባላቸው ባልተገኙበት ረቡዕ ዕለት ቴህራን ውስጥ መፈጸሙ ተዘገበ።
ዛሃራ ሃዳድ አዴል በመጀመሪያው ዕለት ጥቃት ከተገደሉት የኻሜኒ ቤተሰብ አባላት አንዷ ናቸው። በመጀመሪያው ዕለት የቦምብ ጥቃት የኢራን ጠቅላይ መሪ እና ሌሎች በርካታ የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት መገደላቸው ይታወሳል።
በተጨማሪም የአባታቸውን ሥልጣን የተረከቡት የዛሃራ ባለቤት ሞጅታባ ኻሜኒ በጥቃቱ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው በተደጋጋሚ ቢነገርም እስካሁን በተጨባጭ የተረጋገጠ ነገር የለም።
የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ጠቅላይ መሪ ከሆኑ በኋላ የጽሁፍ መልዕክት ከማስተላለፍ ውጪ በይፋ ለሕዝብ ያልታዩት ሞጅታባ በጥቃቱ በደረሰባቸው ከባድ ጉዳት ምክንያት እንደሆነ ይነገራል።
በመጀመሪያው ዕለት ጥቃት የተገደሉት የሞጅታባ ሚስት ዛሃራ የሟቹ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ አማካሪ እና በእስላማዊው ሪፐብሊክ ውስጥ ተደማጭ የሆኑት ጎላማሊ ሃዳድ አዴል ልጅ ነበሩ።
ከጥቂት ቀናት በፊት ጎላማሊ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጥቃት ከከፈቱ ወዲህ የሟች ሴት ልጃቸው ባለቤት የሆኑትን ሞጅታባ ኻሜኒን አግኝተዋቸው እንደማያውቁ ተናግረዋል።